ማክሰኞ 24 ፌብሩዋሪ 2015

አንቲ ውእቱ ተስፋሁ ለአዳም አመ ይሰደድ እምገነት፡- ከገነት በተባረረ ጊዜ የአዳም ተስፋ አንቺ ነሽ

ቅዱስ አባ ሕርያቆስ ዘሀገረ ብሕንሳ
·         “ኪዳነ ተካየድኩ ምስለ ኅሩያንየ፤ ከመረጥሁት ጋር ቃል ኪዳኔን አደረግሁ”
መዝ. 89፡3
·         ኪዳነ ምሕረት ድንግል ማርያም ወላዲተ አምላክ
አምላካዊ ሕግ ወደ ጎን ትቶ በሰይጣን ምክንያት የቀረበለት ፍጹም የሐሰት ሽንገላና ሥጋዊ ፍላጉቱን ተከትሎ አትብላ የተባለውን በልቶ፤ አታድርግ የተባለውን ያደረገው አዳም አባታችን ከፈጣሪ የተሰጡትን አምላካውያን በረከቶች አንድ በአንድ ከላዩ ላይ እየተገፋፉ ርቀው ዕርቃኑን በቀረ ጊዜ የፈጸመው ድርጊት ሥጋዊና ሰይጣናዊ እንዲሁም ፈቃደ እግዚአብሔርን ያልተከተለ መሆኑ ተገንዝቦ በሰውነቱ ላይ ቅጠላ ቅጠልን አገልድሞ ከልቡ ምርር ብሎ አለቀሰ፡፡ ፊቱንም በንስሐ እንባ ታጠበ፡፡
ከክብር ይልቅ ውርደትን፣ ከሕይወት ይልቅ ሞትን፣ ከደስታ ይልቅ ሐዘንን መርጦ በራሱ ፈቃድ በጸጋ ከፈጣሪ የተሰጡት ጸጋዎች መገፈፋቸው ካወቀ በኋላ የፈጣሪው ርህሩህነትና መሐሪነት አብዝቶ ተረድቶ ስለነበረ ሳይውል ሳያድር ንስሐ ገብቶ “አጥፊቻለሁ ይቅር በለኝ” ብሎ ከልቡ ተጸጽቶ የንስሐ ጸሎት አቀረበ፡፡

ምሕረት የባሕርይ ገንዘቡ የሆነ እግዚአብሔርም የንስሐ ጸሎቱን ተቀብሎ ከልጅ ልጅህ ተወልጄ፣ በሞቴና በመስቀሌ ቤዛ ሆኜ አድንሃለሁ በማለት የድኅነት ተስፋ /የድኅነት ቃል ኪዳን/ ሰጠው፡፡
ይህች አማናዊት የደኅነተ ዓለም ተስፋ /ቃል ኪዳን/ ማለትም አስቀድሞ ለአዳም ከልጅ ልጅህ እወለዳለሁ በማለት የሰጠው ተስፋ፣ እግዚአብሔርም ለአዳም የገባለትን የምሕረት፣ የይቅርታ ቃል ኪዳን እውን የሚሆንባት፣ ዘመን የማይቆጠርለት ረቂቁ መለኮት በተዋሕዶ ምስጢር ሥጋ ተዋሕዶ ፍጹም ሰው፣ ፍጹም አምላክ ሆኖ የሚያድርባት አማናዊት ቅድስተ ቅዱሳን፣ አካላዊ ቃል፣ እግዚአብሔር ወልድ፣ ኢየሱስ ክርስቶስ ማኅጸንዋን ዓለም አድርጎ በቅዱሳን መላእክት የሚመሰገንባት እውነተኛ የድኅነት ምልክት ወላዲተ አምላክ ድንግል ማርያም መሆንዋ እውነት ሆነ፡፡ ነቢያት ድንግል ማርያም ትክክለኛ የድኅነታችን ምልክት መሆንዋ አስቀድመው ትንቢት ተናግረዋል፡፡
·         “ስለዚህ ጌታ ራሱ ምልክት ይሰጣችኋል፡፡ እነሆ ድንግል ትፀንሳለች ወንድ ልጅም ትወልዳለች ስሙንም አማኑኤል ብላ ትጠራዋለች” ኢሳ.7፡14
ይህንን አማናዊ ትምህርት አምልቶና አስፍቶ፣ በምስጢርም አገናኝቶ ካስተማሩን አበው አንዱ ብርሃን ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ ነው፡፡ ይኸውም በጥንተ ፍጥረት አዳም በተሳሳተ ጊዜ እግዚአብሔር ሲረግማቸው ለእባብ እንዲህ አለው፡-
·         “ከምድር አራዊት ሁሉ ተለይተህ አንተ የተረገምህ ትሆናለህ፡፡ በሆድህም ትሄዳለህ፤ አፈርም በሕይወትህ ሁሉ ትበላለህ፡፡ በአንተና በሴቲቱ መካከል በዘርህና በዘርዋ መካከል ጠላትነትን አደርጋለሁ፤ እራሱ ራስህን ይቀጠቅጣል አንተም ሰኰናውን ትነክሳለህ” /ዘፍ. 3፡14-15/፡፡
ይህንን የሔዋንና የልጆቿ ምሳሌያዊ ትንቢት የዘመኑ ፍጻሜ በደረሰ ጊዜ በአማናዊት በድንግል ማርያምና በመድኃኒተ ዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ መፈጸሙን ሲያመላክት ማለትም አስቀድሞ ጠላትነቱ ከሴቷ የተባለችው ዳግማዊት ሔዋን ድንግል ማርያም፣ ከእርሷ የሚወለደው ራስህን ይቀጠቅጣል የተባለው ደግሞ ወልደ አብ ወልደ ድንግል ኢየሱስ ክርስቶስ መሆኑን ሲገልጽ ከሴት ተወለደ በማለት ይገልጸዋል፡፡
·         “ነገር ግን የዘመኑ ፍጻሜ በደረሰ ጊዜ እግዚአብሔር ከሴት የተወለደውን ከሕግም በታች የተወለደውን ልጁን ላከ” ገላ. 4፡4 እንዲል፤
·         “ዘንዶውም ወደ ምድር እንደተጣለ ባየ ጊዜ ወንድ ልጅ የወለደችውን ሴት አሳደዳት፣ ከእበቡም ፊት ርቃ አንድ ዘመን፣ ዘመናትም፣ የዘመንም እኩሌታ ወደ ምትመገብበት ወደ ስፍራዋ ወደ በረሃ እንድትበር ለሴቲቱ ሁለት የታላቁ ንሥር ክንፎች ተሰጣት” ራዕ. 12፡13-14 እንዲል፤
የድንግል ማርያም ምስጋና የበዛለት ቅዱስ አባ ሕርያቆስም በቅዳሴ ማርያም አንቀጹ ይህን ትምህርተ ሐዋርያትን መሠረት በማድረግ “አንቲ ውእቱ ተስፋሁ ለአዳም አመ ይሰደድ እም ገነት፡- ከገነት በተባረረ ጊዜ የአዳም ተስፋ አንቺ ነሽ” በማለት ይገልጸዋል፡፡ (ቅዳሴ ማርያም)
የቅዱሳን የምሕረት ቃል ኪዳን
·         “ኪዳነ ተካየድኩ ምስለ ኅሩያንየ፡-ከመረጥኋቸው ጋር ቃል ኪዳኔን አደረግሁ”(መዝ. 89፡3)
አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ “ኪዳን”ን ሲተረጉሙ ውል፣ ቁም ነገር፣ የፍቅርና የአንድነት መሐላ፣ ሰላማዊ ሕግ፣ ሁለቱን ወገን አንድ የሚያደርግ፣ ስለረብና ስለ ጥቅም በተስፋ የቆመ የተጻፈ ሥርዓት፣ ቢያፈሥርሱት ጉዳትና ጠብ የሚያመጣ በማለት ገልጸውታል፡፡ /መጽሐፈ ሰዋሰው ወግስ ወመዝገበ ቃላት ሐዲስ፡ ገጽ 529/
ደስታ ተክለወልድ ደግሞ “ተካየደ”ን ሲተረጉሙ ተዋዋለ፣ ቃል ኪዳን ተጋባ፣ ተማማለ በማለት ይፈቱታል፡፡ /አዲስ ያማርኛ መዝገበ ቃላት ገጽ 243/
ሰውን ለማዳን ቸርነቱ ብዙ የሆነ አምላካችን እግዚአብሔር ለወዳጆቹ፣ ለባለሟሎቹ፣ ለቅዱሳኑ ከሃይማኖታቸው ጽናት፣ ከሕይወታቸው መንፈሳዊነት፣ ከማዕረጋቸው ፍጹምነት፣ ከሥራቸው ምግባር ትሩፋት የተነሳ በቅድስና ክብር አክብሮ እንዲጠሩበት /ቅዱስ እንዲባሉ/ እና እንዲሆኑበት /ቅዱሳን እንዲሆኑ/ ጸጋውን አብዝቶ ከመስጠቱ በተጨማሪ ኃጥአንን ሊያሰምር የሚያስችል የምሕረትና የይቅርታ ቃል ኪዳንም ሰጥቶ አክብሯቸዋል፡፡ ይኸውም ከላይ እንደተገለጸው እግዚአብሔር ራሱ በቅዱስ ዳዊት አድሮ አረጋግጦልናል፡፡ ቅዱስ ሆኖ ቅዱሳን ሁኑ በማለት እንደተናገረን፡፡ ለምሳሌ
ለኖኅ የምሕረት ቃል ኪዳን ተሰጥቶታል፡፡
·         “ቃል ኪዳኔንም ለእናንተ አቆማለሁ ሥጋ ያለውም ሁሉ ዳግመኛ በጥፋት ውኃ አይጠፋም ምድርንም ለማጥፋት ዳግመኛ የጥፋት ውኃ አይሆንም። እግዚአብሔርም አለ፦ በእኔና በእናንተ መካከል፥ ከእናንተም ጋር ባለው በሕያው ነፍስ ሁሉ መካከል፥ ለዘላለም የማደርገው የቃል ኪዳን ምልክት ይህ ነው፡፡ ቀስቴን በደመና አድርጌአለሁ፥ የቃል ኪዳኑም ምልክት በእኔና በምድር መካከል ይሆናል።”  ኦሪት ዘፍጥረት ምዕ.9 11-12
ለአብርሃም የምሕረት ቃል ኪዳን ተሰጥቶታል፡፡፡-
·         “ቃል ኪዳኔንም በእኔና በአንተ መካከል ከአንተም በኋላ ከዘርህ ጋር በትውልዳቸው ለዘላለም ኪዳን አቆማለሁ፥ ለአንተና ከአንተ በኋላ ለዘርህ አምላክ እሆን ዘንድ። … በእኔና በአንተ መካከል፥ ከአንተም በኋላ በዘርህ መካከል የምትጠብቁት ቃል ኪዳኔ ይህ ነው ከእናንተ ወንድ ሁሉ ይገረዝ።”ኦሪት ዘፍጥረት ምዕ. 17:7-10
የቃል ኪዳን ጥቅም (አገልግሎት)
እግዚአብሔር ለቅዱሳኑ የሰጠው የምሕረትና የይቅርታ ቃል ኪዳን የሚያገለግለው ሃይማኖት ገንዘብ አድርገው በምግባር በትሩፋት ለደከሙ ኃጥአን ነው፡፡ የምሕረት ቃል ኪዳን በዋናነት የሚጠቅመው ለኃጥአን ነው እንጂ ለጻድቃን አይደለም፡፡ ምክንያቱም ጻድቃንበጽድቃቸው እና በምግባር ትሩፋታቸው ምሕረትን ያገኛሉና ነው፡፡
·         “አዘክሪ ለኃጥአን ወአኮ ለጻድቃን፤ አዘክሪ ለርሱሐን ወአኮ ለንጹሐን፡- ለጻድቃን ያይደለ ለኃጥአን አሳስቢ፤ ለንጹሐን ያይደለ ለተዳደፉት አሳስቢ” ቅዳሴ ማርያም (ሐዳፌ ነፍስ)
·         “እስመ ለነ ለኃጥአን ለእመ መሐርከነ ትሰመይ መሐሬ፤ ወለጻድቃንስ እምግባሮሙ ትሜሕሮሙ በትዔስዮሙ በከመ ጽድቆሙ፡-እኛን ሐጥአንን ብትምረን ያን ጊዜ መሐሪ ትባላለህና፤ ጻድቃን ግን ከሥራቸው የተነሳ ትምራቸዋለህ፤ እንደጽድቃቸውም ትሰጣቸዋለህ” (ቅዳሴ ዘኤጲፋንዮስ፡ ሐዳፌ ነፍስ)
በዚህ መሠረት ማለትም በቅዱሳኑ ቃል ኪዳን ምክንያት ኃጥአንን ይቅርታንና ምሕረትን አግኝተዋል፡፡ እግዚአብሔርም የገባው የወዳጆቹ ቃል ኪዳን በማሰብ ምሕረትን አድርገዋል፡፡
·         “እንዲህም ይሆናል ይህችን ፍርድ ሰምተህ ብትጠብቃት ብታደርጋትም፥ አምላክህ እግዚአብሔር ለአባቶችህ የማለውን ቃልኪዳንና ምሕረት ለአንተ ይጠብቅልሃል” ኦሪትዘኁልቅ ምዕ. 7፤ 12
·         “ስለዚህም እግዚአብሔር ስለ አሦር ንጉሥ እንዲህ ይላል። ወደዚች ከተማ አይመጣም፥ ፍላጻንም አይወረውርባትም፥ በጋሻም አይመጣባትም፥ የአፈርንም ድልድል አይደለድልባትም።በመጣበት መንገድ በዚያው ይመለሳል፥ ወደዚችም ከተማ አይመጣም ይላል እግዚአብሔር፦  ስለ እኔም ስለ ባሪያዬም ስለ ዳዊት ይህችን ከተማ አድናት ዘንድ እጋርዳታለሁ።  የእግዚአብሔርም መልአክ ወጣ፥ ከአሦራውያንም ሰፈር መቶ ሰማንያ አምስት ሺህ ገደለ ማለዳም በተነሡ ጊዜ፥ እነሆ፥ ሁሉ በድኖች ነበሩ”ትንቢተ ኢሳይያስ ምዕ. 37፤33-34
·         “እግዚአብሔርም የለቅሶአቸውን ድምፅ ሰማ፥ እግዚአብሔርም ከአብርሃምና ከይስሐቅ ከያዕቆብም ጋር ያደረገውን ቃል ኪዳን አሰበ” ኦሪት ዘጸ.2፡24
·         “እግዚአብሔር ግን ራራላቸው፥ ማራቸውም፥ ከአብርሃምና ከይስሐቅ ከያዕቆብም ጋር ስላደረገውም ቃል ኪዳን እነርሱን ተመለከተ ሊያጠፋቸውም አልወደደም፥ ፈጽሞም ከፊቱ አልጣላቸውም”2ኛ መጽ. ነገሥት 13፡23
·         “ነገር ግን ከዳዊት ጋር ስላደረገው ቃል ኪዳን፥ ለእርሱና ለልጆቹም በዘመናት ሁሉ መብራት ይሰጠው ዘንድ ስለ ሰጠው ተስፋ፥ እግዚአብሔር የዳዊትን ቤት ያጠፋ ዘንድ አልወደደም” 2ኛ መጽ. ዜና መዋዕል. 21፡7
ኪዳነ ምሕረት ድንግል ማርያም ወላዲተ አምላክ
እውነተኛውን ፀሐየ ጽድቅ ያስገኘች አማናዊት ሰማይ ድንግል ማርያምም እንደሌሎች ቅዱሳን ሁሉ ኃጥአንን የሚያስምር የምሕረት ቃል ኪዳን የካቲት 16 ቀን ልጇ ወዳጇና ፈጣሪዋ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰጥቷታል፡፡ ይኸውም የምስጢር ድኅነት አማናዊት መቅደስ መሆኗን፣ ለይኩን ብሎ ለፈጠራት አምላክ ይኩነኒ በሚል ቃል ትህትና ምክንያት በተዋሕዶ ምስጢር አምላክ ሰው ሰውም አምላክ እንዲሆን ሆና፣ አህላ፣ በቅታና ነቅታ የተገኘች እመ አምላክ፣ ወላዲተ አምላክ መሆኗን ድንግል በድንግልና አምላክን ጸንሳ የወለደች በዚህም ቅድመ ጸኒስ፣ ጊዜ ጸኒሳ፣ ድኅረ ጸኒስ፤ ቅድመ ወሊድ፣ ጊዜ ወለድ፣ ድኅረ ወሊድ ተፈትሖ ማኅፀን የሌለባት ወትረ ድንግል ማርያም መሆንዋን፣ ንፅሕናዋ ቅድስትናዋ ከፍጡራን በላይ ከፈጣሪ በታች ሆኖ አማናዊት ቅድስተ ቅዱሳን፣ ንጽሕተ ንጹሐን ወላዲተ አምላክ መሆንዋን አምኖ በእውነት ለሚታመናት ሁሉ በስሟ የመታዘዝ ሕይወትን፣ የትሕትና ሕይወትን ገንዘብ አድርጎ ምግባር ትሩፋት የፈጸመ በሰማይ ከፍ ያለ ዋጋ /ዘላለማዊ ሕይወት/ እንደሚያገኝ፣ ሃይማኖት ይዞ ምግባረ ደካማ ቢሆን ድካሙ ተሟልቶለት ማዓረገ ቅድስና አግኝቶ እጣ ፈንታው ጽዋ ተርታው ከቅዱሳን ጋር እንደሚሆን ሁሌም ስለኃጥአን እያለቀሰች ትጸልይበት በነበረ በልጇ መቃብር በጎልጎታ ላይ ልጇ ከቅዱሳን መላእክት ጋር ወርዶ ቃል ገብቶላታል፡፡
መድኃኒታች ኢየሱስ ክርስቶስ “እናንትተን የሚቀበል እኔን ይቀበላል፤ እኔንም የሚቀበል የላከኝን የቀበላል፡፡ ነቢይን በነቢይ ስም የሚቀበል የነቢይን ዋጋ ይወስዳል፤ ጻድቅንም በጻድቅ ስም የሚቀበል የጻድቁን ዋጋ ይወስዳል”(ማቴ.1040-41) በማለት እንዳስተማረን በወላዲተ አምላክ ስም የሚደረግ መንፈሳዊ ምግባር ትሩፋት ሁሉ ሰማያዊ ጸጋና በረከት የሚያስገኝ መሆኑን በማመን ይህንን ዘላለማዊ የምሕረት ቃል ኪዳን በማመንና በመታመን ሃይማኖታዊ አገልግሎታችንን በሚገባ እናከናውነረበታለን፤ በዚህም የኪዳነ ምሕረትን በረከትና ረድኤት ተሳታፊዎች እንሆናለን፡፡
ይህም ዕለት ታላቅ የምሕረት ጸጋ የተገኘበት ስለሆነ ኪዳነ ምሕረት ተብሎ በመስየም ሁሌም በየዓመቱ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በታላቅ መንፈሳዊ አገልግሎት ታከብረዋለች፡፡ እኛ የቤተ ክርስቲያን ልጆችም በስሟ የተራቡትን በማብላት፣ የተጠሙትን በማጠጣት፣ የታረዙትን በማልበስ፣ ደካሞቹን በመርዳት… ዓቅማችን በፈቀደው መልኩ ያለንን ከሌለው ጋራ በማካፈል በዓሉን በሃይማኖታዊ ምግባር ትሩፋት እናከብረዋለን፤ ቅዱስ ጳውሎስ ክብር ለሚገባው ክብር ስጡ (ሮሜ.13:7) ይላልና፡፡
“ስአሊ ለነ ቅድስት”
ጽንዕት በድንግልና ስርጉት በቅድስና እመቤታችን ድንግል ማርያም ወላዲተ አምላክ ልጅሽ ወዳጅሽ ጸጋውን ክብሩን እንዳይነሳን ለምኝልን፡፡

አሜን!!

ምንም አስተያየቶች የሉም:

አስተያየት ይለጥፉ